Monday, March 23, 2015

ሶስቱ አገራት በግድቡ ላይ የተዘጋጀውን የስምምነት ሰነድ ፈረሙ

(መጋቢት 14/2007, (አዲስ አበባ))--ኢትዮጵያ፣ ግብጽና ሱዳን በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ላይ መተማመን እንዲኖር የተዘጋጀውን በመርህ ላይ የተመሰረተ የስምምነት ሰነድ ፈረሙ።



በሱዳን ካርቱም የተደረገውን ስምምነት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ የግብጹ ፕሬዝዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ እና የሱዳኑ ፕሬዝዳንት ኦመር ሃሰን አልበሽር ፈርመዋል።
በስምምነቱ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ እንዳሉት “ኢትዮጵያ እየገነባች ያለችው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ከራሷ አልፎ ግብጽና ሱዳንን ብሎም ሌሎችን አገራትን ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው”። ዛሬ የተፈረመው ስምምነትም ከአገራቱ የትብብር መስኮች አንዱና በተለይም በሶስቱ አገራት መካከል የጋራ ተጠቃሚነትና ልማትን የሚያጠነክር እንደሆነ ተናግረዋል።

“ሁላችንም የአባይ ውሃ ያስተሳሰረን የአንድ ቤተሰብ አባል ነን”ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ“ስምምነቱ በሶስቱ እህትማማች አገራት መካከል ጠንካራ መተማመንን በመፍጠር ግንኙነታችንን ይበልጥ ያሳድገዋል” ሲሉ እምነታቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በግድቡ ላይ መተማመንን ለመፍጠር ቀደም ሲል ታከናውናቸው የነበሩ ስራዎችና የስምምነቱ መፈረም ለጋራ ልማትና ተጠቃሚነት ያላትን ዝግጁነት የሚያሳይ ነው ብለዋል።

“የኢትዮጵያ ልማት ላይ ቅሬታ የለንም፤ ነገር ግን የግብጻውያን ህይወት የአባይ ውሃ ላይ የተመሰረተ በመሆኑ ጠንካራ መተማመን ሊኖረን ይገባል” ያሉት ደግሞ የግብጹ ፕሬዝዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ ናቸው።

ከግብጽ መሪዎች የአባይ ውሃ ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ላይ የተሻለ አቋም የሚያራምዱት ፕሬዝዳንት አልሲሲ ባለፉት ዓመታት በመንግስታትና ህዝቦች መካከል መተማመን ርቆ መቆየቱን አስታውሰው"ህዝቦቻችንን በአዲስ መልኩ መወከል ስላለብን ለቀጣይ ጉዞ ትብብርን መርጠናል" ብለዋል። "አገራቱ በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ስምምነቶችን ፈርመዋል፤ ይኸኛው ግን ታሪካዊ ነው"ሲሉ የስምምነቱን ታላቅነት የገለጹት አልሲሲ በሙሉ ልባችን ልንተማመን ይገባናል ነው ያሉት።

"ካርቱም ይኸን መሰል ታሪካዊ ስምምነት በማስተናገዷ ደስተኛ ነን"ሲሉ የገለጹት የሱዳኑ ፕሬዝዳንት ኦመር ሀሰን አልበሽር በበኩላቸው ስምምነቱ ለቀጣይ ጉዞ መሰረት የሚጥል እንደሆነ ተናግረዋል። ግድቡ በአገራቱ ላይ ተጽዕኖ እንደማይኖረው መተማመን የሚፈጥርና ግንኙነቱን የሚያጠናክር እንደሚሆንም እምነታቸውን ገልጸዋል።

በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ላይ መተማመን ለመፍጠር የተዘጋጀውን ሰነድ በካርቱም የፈረሙት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም አዲስ አበባ ተመልሰዋል። ማምሻውን አዲስ አበባ የገቡት የግብጹ ፕሬዝዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲም በግድቡ ዙሪያ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝና ከፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋር ውይይት እንደሚያደርጉ ይጠበቃል።

ግንባታ የጀመረበትን አራተኛ ዓመት መጋቢት 24 ቀን 2007 ዓም የሚደፍነው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ስራው ከ42 በመቶ በላይ መከናወኑ ይታወቃል።
ምንጭ:  ኢዜአ

No comments:

Post a Comment