Tuesday, October 21, 2014

«ፀረ ሰላም ኃይሎች የአሜሪካ መንግሥት ዝም ብሎናልና ይደግፈናል ብለው ካሰቡ ተሳስተዋል»

(Oct, 21, 2014, (አዲስ አበባ))--የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ በቅርቡ በኢፌዴሪ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለሁለቱ ምክር ቤቶች አባላት ያደረጉትን የመክፈቻ ንግግር ተከትሎ በምክር ቤቱ አባላት ለቀረቡ ሞሽኖች ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ሰሞኑን ምላሽ መስጠታቸው ይታወቃል። በተለይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከፓርላማው አባላት ለቀረቡ ሃሳቦች ፖለቲካዊ በሆኑ ጉዳዮች የተነሱ ጥያቄዎችና ማብራሪያቸው እንደሚከተለው ቀርቧል።

ጥያቄ፡- ኢትዮጵያ በሁለትዮሽም ሆነ ባለ ብዙ ወገን መድረኮች ላይ ያላትን ተሰሚነት ከማሳደግ አኳያ በዲፕሎማሲው መስክ የምታደርጋቸው እንቅስቃሴዎች በምን ደረጃ ላይ ይገኛሉ?

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም፡- ዋናው የዲፕሎማሲያችን እምብርት የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ነው። ይህን መንግሥት በፖሊሲው በሚገባ አስቀምጧል። ይህንንም ያደረገበት ዋናው ምክንያት በተደጋጋሚ እንደሚገለጸው ዋናው ጠላታችን ድህነት መሆኑ ስለተረጋገጠና ተጋላጭነታችንም ከውስጥ የሚመነጭ ተጋላጭነት ነው የሚል ፅኑ እምነት በፖሊሲያችን ስላለ ነው።

ከዚህ አኳያ ከአገሮች ጋር የምናደርገው ግንኙነት፣ የፖለቲካ ዲፕሎማሲም ሆነ የሕዝብ ለሕዝብ ዲፕሎማሲ የሚመራው በኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ነው። ፖለቲካውም እንዲሻሻል የምንፈልገው ኢኮኖሚያችንን ለማሳደግ ነው። የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነታችንም እንዲጠናከር የምናደርገው ኢኮኖሚያችንን ለማሳደግ ነው። ከጎረቤቶቻችን ጋር በሰላምና በፍቅር በኢኮኖሚ መሠረተ ልማቶች ተሳስረን እንሂድ የምንለው የኢኮኖሚ ትብብራችን እንዲጎለብት ነው፤ በጋራ ለማደግ ስለሚያግዘንም ነው። የፀጥታና ደህንነት ጉዳዮችን በተመለከተ ኢትዮጵያ ተግታ የምትሠራው ለኢኮኖሚ ዲፕሎማሲያችን ካለው ፋይዳ አኳያ እየመዘነች እንደሆነም ሊታወቅ ይገባል።

ጥያቄ፡- ኢትዮጵያ ከአሜሪካ ጋር ታሪካዊ ግንኙነት እንዳላት ይታወቃል። በቅርቡ ደግሞ በእርስዎና በፕሬዚዳንት ባራክ ሁሴን ኦባማ የተደረገው የሁለትዮሽ ውይይት ምን ያክል ጠቀሜታ ያለው ነው? በሁለቱ መንግሥታት መካከል በልዩነት የተነሱስ ነጥቦች ነበሩ?

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም፡- ቀደም ሲል ለመግለፅ እንደሞከርኩት ከአሜሪካ መንግሥት ጋርም ያደረግነው የሁለትዮሽ የጋራ ውይይት በኢኮኖሚያዊ ዲፕሎማሲ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ለመድረስ ነው፤ በዚህ ዙሪያም ነው የተስማማነው። የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ሁሴን ኦባማ እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ ከቦይንግ በርካታ አውሮፕላኖችን በመግዛት ለአሜሪካውያን የሥራ ዕድል መፍጠር ጀምራለች። በተመሳሳይ የአሜሪካ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ኢንቨስት ሲያደርጉ ለኢትዮጵያውያንም የሥራ ዕድል ይፈጥራሉ።

ዋነኛው የመልዕክታችን እምብርት የሆነው የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ነው። በዚህ ዙሪያ ኢኮኖሚያችን ሰላም ሲኖር ነውና የሚረጋገጠው የአካባቢ ሰላምን በተመለከተ ኢትዮጵያ በምትጫወተው ሚና በጋራ ለመስራት የሚያስችል ስምምነት ላይ ከአሜሪካ ጋር ደርሰናል። ከዚያም አልፎ አሸባሪዎችንና ፀረ ሰላም ኃይሎችንም በመዋጋቱ ላይ በጋራ እንደምንሰራ ተስማም ተናል።

ፀረ ሰላም ኃይሎች የአሜሪካ መንግሥት ዝም ብሎናልና ይደግፈናል ብለው የሚያስቡ ከሆነ ተሳስተዋል። ስለዚህ እኛ ፀረ ሰላም ኃይሎችን አደብ ለማስገዛት የምንሠራውን ሥራ በተመለከተ በግልጽ አቅርበን ፀረ ሰላም ኃይሎችና ሕገ ወጥ የሆኑ ማናቸውም አካላት በሕግ መጠየቅ የመንግሥት ግዴታ በመሆኑ ላይ ስምምነት አለን።

በጥቅሉ ከአሜሪካ መንግሥት ጋር የተደረገውን ውይይት ያለአንዳች ልዩነት ግንኙነታችንን ከፍ ለማድረግ የሚያስችል ሁኔታን የፈጠረ ነው። በሁለታችንም መካከል የተነሱ ነጥቦች ላይ ምንም ዓይነት ልዩነት ያልነበረው እንደሆነ መግለጽ እፈልጋለሁ።

ጥያቄ፡- ኢትዮጵያ ዓለም አቀፉ የወንጀል ፍርድ ቤት (አይ.ሲ.ሲ) ወንጀለኞችን ለፍርድ በማቅረብ ስም በአፍሪካውያን ላይ የሚ ያደርገውን ዘመቻ በግንባር ቀደምትነት ስትቃወም ቆይታለች። በኬንያው ፕሬዚዳንት ላይ የተመሠረተው ክስ እንዲሰረዝ በማድረጉ ሒደት መሻሻል የታየ ቢመስልም በፍርድ ቤቱ ቀርበዋልና ይህ እንዴት ይታያል?

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም፡- ተቋሙ አፍሪካውያን ላይ ያለውን ጥላቻ ኢትዮጵያ ገና ከመጀመሪያው ስለተገነዘበች የተቋሙ አባል አይደለችም። ለምክር ቤቱ እንደ መረጃ ያገለግል ዘንድ የዚህ ተቋም አባል ያልሆኑት የዓለም ሁለት ሦስተኛ ሕዝቦችን የያዙ አገሮች ናቸው። አብነት መጥቀስ ካስፈለገ አሜሪካ፣ ሩሲያ፣ ቻይና፣ ሕንድና ሌሎችም የላቲን አሜሪካ አገሮች አባል አይደሉም።

አውሮፓውያንና ቅኝ ተገዥ ዎች የነበሩ አፍሪካውያን ናቸው በዚህ ተቋም የገቡት። ይህ ተቋም አፍሪካ ውስጥ የሰብአዊ መብት ረገጣ እንዳይኖር የሚል በጎ ሃሳብ፣ አመለካከትና እርምጃ ብቻ ከፊት ለፊቱ አስቀምጦ ነገር ግን ጭንብል በለበሰ አኳኋን የአፍሪካ መሪዎችን የሚያሳድድ ተቋም ሆኖ ነው የተገኘው።

ብዙዎች የአፍሪካ መሪዎች ከዚህ ተቋም ለመሸሽ የሚፈ ልጉት «የሰብአዊ መብት ረገጣ ስለሚያካ ሂዱ ፈርተው ነው» የሚል ሃሳብ ያቀርባሉ። ሰብአዊ መብት ረገጣ የሚካሄደው በአፍ ሪካ ብቻ ነው ያለው ማነው? ስለዚህ የአፍሪካ ህብረትና የአፍሪካ መንግሥታት ሰብአዊ መብትን ለመጠበቅና ጥሰትን ለመከላከል የራሳቸውን ሕግ አውጥተዋል። የአፍሪካ ህብረት ከሚሠራቸው ዋነኛ ጉዳዮች አንዱ የሰብአዊ መብት ረገጣ በሚኖርበት ጊዜ አገሮቹ ውሰጥ ጣልቃ እስከመግባት መሄድ የሚያስችል ሕግ አውጥ ቷል።

ስለዚህ የአፍሪካ መሪዎች በሰብአዊ መብት ረገጣ መከላከል ቁርጠኝነት ላይ ሊከሰሱ አይች ሉም። የትም የሰብአዊ መብት ረገጣ ሲኖር የአፍሪካ መሪዎች ለዚህ ተቃራኒ ሆነው ይቆማሉ፤ እንዲጠየቁም ያደርጋሉ። ነገር ግን አሁን በተግባር እየታየ ያለው 99 በመቶ ያህሉ በፍርድ ቤቱ የሚቀርቡት አፍሪካውያን ናቸው። ስለዚህ ይህ ጉዳይ መታረም አለበት የሚል ፅኑ እምነት ያለው የአፍሪካ ህብረት ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያም ጭምር ናት።

ጥያቄ፡- አሁን ባለው ሁኔታ በአንድነት ፓርቲ ውስጥ ንቁ ተሳትፎ የሚያደርጉ ወጣቶ ችን ለሰላማዊ ለውጥ የሚተጉ ብሎገሮችን ማንገላታት ለዚህች አገር የሚጠቅም አይደለም። ጋዜጠኞችንም ማሰር እንዲሁ፤ ስለዚህ ይህ የፖለቲካ መፍትሔ ያሻዋልና እንዴት ይታያል?

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም፡- የህትመት ሚዲያዎች በፕሬስ ሕጉ መሠረት የሙያ ሥነ ምግባራቸውን ጠብቀው መሥራት እንዳለባቸው ይታወቃል። አንዳንዶች ከሙያ ሥነ ምግባራቸው ውጪ በሕዝቦች መካከል ጥላቻ እየዘሩ አመፅና ብጥብጥ እንዲከናወን ለማድረግ የሚያደርጉት እንቅስቃሴ በግልፅ ለተወሰነ ጊዜ ታግሰን ያየናቸውም ቢሆን ነገር ግን ይሻሻላሉ ብለን ያሰብነው ስላልተሳካ ወደ ሕግ እንዲቀርቡ ተደገናል። ያ ደግሞ በሕግ መስመር የሚይዝበት ሁኔታ ይፈጥራል።

በትክክለኛው መንገድ እየሰሩ ያሉ የህትመት ሚዲያዎችን በተመለከተም በመንግሥት ሊሰጡ በሚገቡ መረጃዎች ላይ ችግር አለብን፤ ስለሆነም የመንግሥት ባለሥልጣናት ለእነዚህ ሚዲያዎች በመረጃ ነፃነት ሕግ መሠረት በራቸውን ክፍት አድርገው ለህትመት ሚዲያዎች የሚሆኑ መረጃዎችን የመስጠት ግዴታ እንዳለብን መረዳት ይገባናል።

ይህን ግዴታ የሚወጡ መስሪያ ቤቶችና ኃላፊዎች ያሉትን ያህል በራቸውን ጠርቅመው የተቀመጡ የመንግሥት ኃላፊዎች እንዳሉም በግምገማችን አስተውለናል። ስለዚህ የግል ሚዲያዎች በተለይም ጤናማዎቹ የግል ሚዲያዎች መረጃ ለእነርሱ ዋነኛ ምንጭ በመሆኑ ይህን አስፈላጊ መረጃ በመስጠቱ ዙሪያ ኃላፊዎችም ሆኑ መስሪያ ቤቶች ትልቅ ኃላፊነት እንዳለባቸው እንዲያውቁ ምክክር ስላደርግን በዚህ የምንቀጥል ይሆናል። ስለሆነም በዚህ በኩል ያለውን ችግር ማስወገዱ አንደኛው ሚዲያ እንዲጎለብት ለማድረግ በመንግሥት በኩል ሊሰራ የሚገባ ጉዳይ ነው የሚሆነው። ይህንንም አጠናክረን እንቀጥላለን። ከዚያ ባሻገር አቅማቸውን ለማጎልበት በየጊዜው ተባብረን የምንሠራ ይሆናል።
ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ, አዲስ አበባ

No comments:

Post a Comment